የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያ የምታከናውነውን የዘላቂ ሰላምና ልማት ተግባራት እንደሚደግፍ ተመድ አስታወቀ

By Meseret Awoke

July 16, 2022

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 9፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ የዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካትና ዘላቂ ሰላምን እውን ለማድረግ የምታከናውናቸውን ተግባራት እንደሚደግፍ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስታወቀ፡፡

በኒዮርክ ከሚካሄደው የዘላቂ የልማት ግቦች ግምገማ ጎን ለጎን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዶክተር ፍጹም አሰፋ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሃፊ አሚና መሃመድ ጋር ተወያይተዋል፡፡

በዉይይቱ ሚኒስትሯ ፥ ኢትዮጵያ በተለያዩ ተግዳሮቶች ውስጥ ብትሆንም ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ እያከናወነች ያለውን ሁሉን አቀፍ ተግባራት አብራርተዋል፡፡

ኢትዮጵያ ከተጋረጡባት ፈተናዎች ሁሉ ትገዝፋለች ያሉት ሚኒስትሯ ፥ መንግስትና ህዝብ በጋራ በሚያከናውኑት የተቀናጀ የትብብር ስራዎች ወደ ብልጽግና ትሻገራለች ሲሉ ገልጸዋል፡፡

የመንግስታቱ ድርጅት ምክትል ዋና ጸሃፊ አሚና ሞሃመድ በበኩላቸው ፥ ኢትዮጵያ የዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት እያከናወነች ያለችውን ተግባራት አድንቀዋል፡፡

ሀገሪቱ አሁን ያለችበትን ሁኔታ እንደሚገነዘቡ የገለጹት ምክትል ዋና ጸሃፊዋ ፥ የልማት ግቦቹን ለማሳካትና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ ኢትዮጵያ ለምታከናውናቸው ተግባራት ድርጅቱ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!