አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 8፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በህልውና ዘመቻው ወቅት ቁስለኞችን ያከሙና ጉዳት የደረሰባቸውን ጀግኖች የተንከባከቡ የአየር ኃይል የጤና ባለሙያዎች ምስጋናና ክብር ይገባቸዋል ሲሉ የአየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌ/ጀኔራል ይልማ መርዳሳ ተናገሩ፡፡
በሀገራዊ ህልውና ዘመቻው ግዳጃቸውን በብቃት ለተወጡ የጤና ባለሙያዎችና ድጋፍ ሰጪ አካላት የምስጋናና የእውቅና ስነ ስርዓት ተካሂዷል፡፡
የአየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ በእውቅና ስነ ስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር ÷ በገጠመን የህልውና ጦርነት ወቅት ኢትዮጵያን ከመፍረስ ለመታደግ ሲሉ ውድ አካላቸውን ለሰጡና ጀግኖች የጦር ጉዳተኞቻችን ተገቢውን የህክምና ክትትል በማድረግ ኃላፊነታቸውን የተወጡ የአየር ኃይል ጤና ባለሙያዎች የላቀ ምስጋናና ክብር ይገባቸዋል ብለዋል።
በውስን ሀብት፣ ጉልበትና እውቀት ለላቀ ለውጥ እንተጋለን የሚለውን የተቋሙን መርህ በመከተል የአየር ኃይል ጤና ማዕከል ያከናወናቸው ተግባራት በአርአያነት እንደሚጠቀስም ገልጸዋል፡፡
የአየር ኃይል ጤና መምሪያ ኃላፊ ብርጋዴር ጀኔራል ዳዲ አስፋው በበኩላቸው÷ መምሪያው የሰራዊቱን አባላትና የቤተሰቡን ጤና የመጠበቅ ተልዕኮን በተሻለ ጥራት እየተወጣ ነው ማለታቸውን የመከላከያ ሰራዊት መረጃ ያመላክታል፡፡
እውቅና የተሰጣቸው የጤናባለሙያዎችና ድጋፍ ሰጪ አካላት በሰጡት አስተያየት÷ እውቅናና ሽልማቱ ለቀጣይ ተልዕኳቸው የበለጠ መነሳሳት እና አቅም እንደሚፈጥርላቸው ገልጸዋል፡፡
ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!