ዓለምአቀፋዊ ዜና

የቦሪስ ጆንሰንን አመራር በመቃወም ሁለት የእንግሊዝ ሚኒስትሮች ሥራቸውን ለቀቁ

By Mikias Ayele

July 06, 2022

የቦሪስ ጆንሰንን አመራር በመቃወም ሁለት የእንግሊዝ ሚኒስትሮች ሥራቸውን ለቀቁ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 29፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የብሪታኒያ ጤና ሚኒስትር ሳጂድ ጃቪድ እና የፋይናንስ ሚኒስትሩ ሪሺ ሱናክ የጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰንን አመራር በመቃወም ሥራቸውን በፈቃዳቸው ለቀዋል።

ሳጂድ ጃቪድ ከእንግዲህ በቦሪስ ጆንሰን መንግስት ሥራዬን በቅንነት ለመሥራት ኅሊናዬ አይፈቅድልኝም ያሉ ሲሆን ፣ ሱናክ ደግሞ ለመልቀቃቸው በምክንያትነት ያነሱት የመንግስትን የብቃት ማነስ ነው ተብሏል።

ሳጂድ ጃቪድ ÷ ወግ አጥባቂው የቦሪስ ጆንሰን ፓርቲ በሕዝብ ዘንድ ተወዳጅነቱን እንዳጣና ሀገራዊ ጥቅም በማስከበር ረገድም ብቃት እንዳነሰው በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ጠቅሰው ጉዳዩን ከሥራ ለመልቀቃቸው በምክንያትነት አንስተዋል።

የሀገሪቷ የፋይናንስ ሚኒስትር ሪሺ ሱናክ ÷ከሥራ ለመልቀቅ ያስገደዳቸው ዜጎች ከቦሪስ ጆንሰን መንግስት ይጠብቁ የነበረው አስተዳደር ከዕውነታው ጋር ባለመጣጣሙ እና በብቃት መምራት ባለመቻላቸው መሆኑን ሺንዋ ዘግቧል፡፡