Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

በሱዳን ወታደራዊ አስተዳደሩን በመቃወም በተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ እስካሁን አራት ሰዎች ለኅልፈት ተዳርገዋል

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 23 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ሱዳን ወታደራዊ አስተዳደሩን በመቃወም በወጡ ሰልፈኞች ተቃውሞ ስትናጥ ውላለች።

አሁንም በቀጠለው የተቃውሞ ሰልፍ እስካሁን አራት ሰዎች ለኅልፈት መዳረጋቸውን የሱዳን ዶክተሮች ማዕከላዊ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

ማዕከላዊ ኮሚቴው ሰልፈኞቹ በኦምዱርማን ከተማ በተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ከፀጥታ ኃይሎች በተተኮሰ ጥይት መመታታቸውንም ነው ያስታወቀው።

ወታደራዊ አስተዳደሩም “የሚሊየኖች ተቃውሞ” በሚል የተነሣውን ሰልፍ በሀገሪቱ ዳግም መፈንቀለ መንግስት እንዳያስከትል በመፍራት የስልክና የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲቋረጥ አድርጓል ነው የተባለው።

የተቃውሞ ሰልፉን የሱዳን ተቃዋሚ ኃይሎች እና ማህበረሰብ አንቂዎች የጠሩት ሲሆን የሰልፉ ዋነኛ አላማም ወታደራዊ ኃይሉ ስልጣኑን ወደ ሲቪል እንዲያሸጋግር ለመጠየቅ ነው ተብሏል።

ከዚህ ባለፈም በፈረንጆቹ 2019 በተነሳው ተቃውሞ በፀጥታ አካላት ለተገደሉ ንጹሃን ፍትህ ለመጠየቅ ያለመ መሆኑም ነው የተነገረው።

በሰልፉ ለኅልፈት ከተዳረጉት በተጨማሪ በርካቶች መቁሰላቸውን አልጄዚራ የማዕከላዊ ኮሚቴውን መረጃ ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

 

Exit mobile version