Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

ቱርክ በኤሌክትሪክ ኃይል ለሚሠሩ ተሽከርካሪዎች የመሠረተ-ልማት ዝርጋታ ልታካሂድ መሆኑን ገለጸች

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 20 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ቱርክ እስከ ፈረንጆቹ 2030 በኤሌክትሪክ ኃይል ለሚሰሩ ተሽከርካሪዎች የሚውሉ የመሠረተ ልማት ዝርጋታዎችን ለማከናወን መዘጋጀቷን አስታውቃለች፡፡

ቱርክ ከኤሌክትሪክ መሠረተ-ልማት ዝርጋታዎች በተጨማሪ የታዳሽ ኃይል ቴክኖሎጂዎችን ለማበልፀግ የሚውል በድምሩ የ3 ቢሊየን ዶላር መዋዕለ-ነዋይ ለማፍሰስ ማቀዷም ነው የታወቀው፡፡

የሀገሪቷ የኤሌክትሪክ ሥርጭት ሥርዓት ኦፕሬተሮች ማኅበር ባዘጋጀው ሥብሰባ ላይ የቱርክ የኃይል እና የተፈጥሮ ሐብት ሚኒስትር ፋቲህ ዶንሜዝ ተገኝተው ነበር።

ፋቲህ ዶንሜዝ ÷ በመጪዎቹ ዓመታት ዋና የመነጋገሪያ ርዕሰ ጉዳይ ከሚሆኑ ነገሮች መካከል አንዱ የሚሆነው የኤሌክትሪክ መኪናዎች ናቸው ሲሉ በሥብሰባው ላይ ተናግረዋል ፡፡

ቱርክ ከፈረንጆቹ 2016 እስከ 2020 ድረስ 4 ነጥብ 5 ቢሊየን ዶላር አካባቢ ለኤሌክትሪክ ኃይል ሥርጭት መሠረተ-ልማት ማስፋፊያ ማዋሏን ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡

እስከ ፈረንጆቹ 2025 ደግሞ 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ዶላር አካባቢ ለመሥመር ዝርጋታ እና ለሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ለማዋል ማቀዷ ነው የተገለጸው፡፡

እስካሁን ቱርክ 1 ነጥብ 2 ቢሊየን ዶላር አካባቢ ለኤሌክትሪክ መሥመር ዝርጋታ ሥራ እንዲሁም ለሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች መጠቀሟን አናዱሉ ዘግቧል፡፡

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
Exit mobile version