የሀገር ውስጥ ዜና

በምስራቅ አፍሪካ ሀገራት መካከል የባሕል ፌስቲቫል ለማካሄድ ከኤምባሲ ተወካዮች ጋር ውይይት ተካሄደ

By Alemayehu Geremew

April 01, 2022

አዲስ አበባ፣መጋቢት 23፣2014 (ኤፍ ቢሲ) የምስራቅ አፍሪካ ህዝቦች የባሕል ፌስቲቫል ለማካሄድ የታላላቅ ሐይቆች እና የአፍሪካ ቀንድ ሀገሮች የኤምባሲ ተወካዮች ጋር ውይይት ተካሄደ።

የባሕልና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ቀጄላ መርዳሳ ÷ የባሕልና የኪነ-ጥበብ ዝግጅት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን ለመገንባት እና በአገሮች መካከል ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ውህደትን ለማጎልበት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በመድረኩም በክብር እንግድነት የተገኙት የኢፌዲሪ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በመክፈቻ ንግግራቸው ÷ ተሳታፊ አገሮችን በማመስገን በምስራቅ አፍሪካ አገራት መካከል የባሕል ፌስቲቫል መካሄዱ የአገራቱን የህዝብ ለህዝብ የግንኙነት ለማጠናከር ወሳኝ እንደሆነ ገልጸዋል።

ለተሳታፊዎቹ ስለ ምስራቅ አፍሪካ ባሕል ፌስቲቫል የባሕልና ስፖርት ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት ኃላፊው አቶ አሕመድ ሙሐመድ ገለጻ አድርገውላቸዋል።

በውይይቱ የምስራቅ አፍሪካን አገሮች የባሕልና የኪነ ጥበብ ፌስቲቫልና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት መድረክ በኢትዮጵያ ለማካሄድ የጋራ መግባባት ላይ ተደርሷል።

ዝግጅቱን ኢትዮጵያ ለማካሄድ ተነሳሽነት መውሰዷን ያደነቁት የሀገራቱ ተወካዮች የክፍለ አህጉራቱን ትሥሥር እና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት እንዲያጠናክር በአንድ ጊዜ ተከናውኖ መቆም እንደሌለበት እና ከየሀገራቱ የባሕል ሚኒስትሮች ጋር በምክክር በየዓመቱ ሀገራት ኃላፊነት ወስደው የሚያካሂዱት ፌስቲቫል እንዲሆን ሃሳብ ማቅረባቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡