የሀገር ውስጥ ዜና

የአገልግሎት ጊዜ ያለፈባቸውን መድሃኒቶች ሲያሰራጩ የተገኙ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ዋሉ

By Tibebu Kebede

February 26, 2020

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 18 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ህጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው የአገልግሎት ጊዜ ያለፈባቸውን መድሃኒቶች ሲያሰራጩ የተገኙ 13 ካናዳውያን እና 2 ኢትዮጵያውያን ዜጎች በቁጥጥር ስር ዋሉ።

በጎንደር ከተማ አስተዳደር የ3ኛ ፖሊስ ጣቢያ ሀላፊ ዋና ሳጅን ደሳለኝ አበራ ለጣቢያችን እንደተናገሩት፥ ግለሰቦቹ በትናንትናው እለት በቁጥጥር ስር ውለዋል።

ህብረተሰቡ ባደረገው ጥቆማም ግለሰቦቹ ማራኪ ክፍለ ከተማ በሚገኘው ልዑል አለማየሁ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት መድሃኒቶቹን ሲያሰራጩ እንደተያዙም ተናግረዋል።

ግለሰቦቹ የህክምና ሙያ እና ህክምናውን መስጠት የሚያስችል ህጋዊ ፈቃድ የሌላቸው መሆኑን የገለጹት ሃላፊው፥ ከ2 እስከ 10 ዓመት የአገልግሎት ጊዜ ያለፈባቸውን መድሃኒቶች መያዛቸውንም ነው የተናገሩት።

አሁን ላይም ከተለያዩ አካላት በተውጣጣ ቡድን ምርመራ መጀመሩንም ጠቅሰው፥ ህብረተሰቡ ለመሰል ህገወጥ ተግባራት ተባባሪ እንዳይሆን ጥሪ አቅርበዋል።

በምናለ አየነው

ትኩስ መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት የቴሌግራም ገፃችንን ሰብስክራይብ ያድርጉ! https://t.me/fanatelevision