የሀገር ውስጥ ዜና

በኮሙኒኬሽን ዘርፍ አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ የጋራ ግንዛቤ ለመፍጠር ያለመ መድረክ እየተካሄደ ነው

By Meseret Awoke

March 19, 2022

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 10፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በኮሙኒኬሽን ዘርፍ አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ የጋራ ግንዛቤ ለመፍጠር ያለመ መድረክ በቢሾፍቱ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።

በመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በተዘጋጀው በዚሁ መድረክ ላይ የክልል የኮሙኒኬሽን ቢሮ ሃላፊዎች፣ የመገናኛ ብዙሃን ሃላፊዎች፣ የፌዴራል ሚኒስትር መስሪያ ቤቶች የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሮች እየተሳተፉ ነው።

የውይይት መድረኩን በንግግር የከፈቱት የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሀላፊ ሚኒስትር ዶክተር ለገሰ ቱሉ ፥ የመንግስት ኮሙኒኬሽን የተሻለ የሕዝብ አገልግሎት ለመስጠት በአዲስ መልኩ መደራጀቱን ገልጸዋል።

የመድረኩ ዓላማም በየዘርፉ የሚገኙ የኮሙኒኬሽን እና የሕዝብ ግንኙነት አካላት በሚሰጧቸው አገልግሎቶች ዙሪያ የጋራ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ለማድረግ ነው ብለዋል።

ዘርፉ የሚሰራው ስራ መንግስት ከሚተገብራቸው የማሕበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ግቦች ጋር የተሳሰረ እንዲሆንና የዘርፉ ተዋናዮች ስራቸውን በብቃት እንዲወጡ ግንዛቤ መፍጠርም ሌላኛው የመድረኩ ዓላማ ስለመሆኑም ተናግረዋል።

በተጨማሪም በዘርፉ እስከ አሁን የገጠሙ ተግዳሮቶችን በመገምገም የመፍትሔ አቅጣጫ ማስቀመጥም የመድረኩ ዓላማ መሆኑንም ጠቁመዋል።

በሕዝብ መካከል ያለውን ትስስር በማጠናከር ዘላቂ ሰላም እና ብልጽግና እንዲረጋገጥ መስራት ከኮሙኒኬሽን አካሉ የሚጠበቅ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ሕብረ-ብሔራዊ አንድነትን የሚያስተናግድ፣ የሚያጎለብቱ እና በሚያረጋግጡ መሠረታዊ ዕቅዶች ላይ በመመርኮዝም ለወደፊቱ ስራዎች እንደሚሰሩ መናገራቸውን ኢዜአ ዘገቧል።

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!