የሀገር ውስጥ ዜና

በቄለም እና ምስራቅ ወለጋ ዞኖች በተካሄደ ኦፕሬሽን 66 የሸኔ ታጣቂዎች ተያዙ

By Alemayehu Geremew

February 01, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥር 24፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኦሮሚያ ፖሊስ፣ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል ፣ የሀገር መከላከያ ሠራዊት እና የፌደራል ፖሊስ በመቀናጀት በአሸባሪው የሸኔ ቡድን ላይ ባካሄዱት ኦፕሬሽን 17 የቡድኑ ታጣቂዎች መማረካቸውንና 49ኙ ደግሞ መያዛቸውን የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ገለጸ፡፡

በኦፕሬሽኑ አኩሪ ውጤት እየተገኘ እንደሆነ እና ጠላት ሲጠቀምባቸው የነበሩ የተለያዩ የጦር መሳሪያዎች እና ተተኳሽ ጥይቶች መያዛቸውም ነው የተመለከተው፡፡

አሸባሪ ቡድኑ ከመንግስት ከህዝብ የዘረፋቸውን የተለያዩ መኪኖች ማቃጠሉም ነው የተመለከተው፡፡

አሸባሪ ቡድኑ ሲጠቀምባቸው የነበሩ በርካታ በርሜል የመኪና ነዳጅ ፣ 2 ጀነሬተር፣ 7 የሞተር ሳይክሎችም መያዛቸውን የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ገልጿል፡፡

የተለያዩ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ መገልገያዎች፣ ዲሾች እና ቴሌቪዥኖች መያዛቸውም ነው የተጠቆመው።

በማፅዳት ዘመቻው ታርጋ ቁጥሩ 3-አ/አ 79852 የሆነ የቤት መኪና እና ታርጋ ቁጥር 33821 የሆነ “አይሱዙ” ተሸከርካሪ 5 ሺህ 895 የክላሽ እና 22 ሺህ 132 የብሬን ጥይት ከ4 ጫኝና አውራጅ ተጠርጣሪዎች ጋር ከአዲስ አበባ ወደ ምስራቅ ወለጋ ሊጓዙ ሲሉ በቁጥጥር ስር መዋላቸውንም ኮምሽኑ ገልጿል፡፡

በተጨማሪም ሁለት የአሸባሪው ሸኔ ቡድን አባላት የክላሽ መሳሪያዎቻቸውን ቀብረው ወደ ነቀምቴ ከተማ ሲሄዱ በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡

አሸባሪውን ሸኔ የማፅዳቱ ዘመቻ ከፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን አመላክቷል፡፡

በዓለማየሁ ገረመው