የሀገር ውስጥ ዜና

አገር አቀፍ የህግ አውጪዎች የጋራ የምክክር መድረክ እየተካሄደ ነው

By Meseret Awoke

January 29, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥር 21፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ለሁለት ቀናት የሚቆይ አገር አቀፍ የህግ አውጪዎች የጋራ የምክክር መድረክ በቢሾፍቱ ከተማ እየተካሄደ ነው።

የህዝብ ተወካዩች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ አቶ ታገሰ ጫፎ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፥ ከዚህ በፊት በፌደራል እና በክልሎች ያለው ግንኙነት ግልፅ ያልነበረ እና ለአሰራር አስቸጋሪ የነበረ መሆኑን አንስተዋል።

በመሆኑም ባለፈው ዓመት የወጣውን አዋጅ መሰረት በማድረግ የፌደራል እና የክልል የህግ አውጪ አካላት የጋራ የምክክር መድረክ ለመጀመሪያ ጊዜ በዛሬው ዕለት መካሄድ መጀመሩን ገልጸዋል።

መድረኩ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን በአግባቡ ለመፈፀም ያግዛልም ብለዋል።

ቀደም ሲል የክልል እና የፌደራል ምክር ቤቶች ዓለም አቀፍ የፖርላማ አሰራሮችን መሰረት በማድረግ ሲንቀሳቀሱ ቆይተዋል ያሉት አፈ ጉባኤው፥ መድረኩ ከሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት ምክር ቤቶች በአግባቡ ስራቸውን እንዲሰሩና አሰራሮችን ለማዘመን የሚያግዝ መሆኑንም ተናግረዋል።

ሀገራችንን ለማፍረስ የተቃጣብን ሴራ ከሽፎ ይህን መድረክ ለማካሄድ በመቻላችን፥ ለዚህ ያበቁን የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ የፀጥታ ሃይሎችና ህዝባችን ምስጋና ይገባቸዋል ብለዋል።

በመድረኩ የክልል እና የፌደራል ምክር ቤት አፈ ጉባኤዎች እና የምክር ቤት ቋሚ ሰብሳቢዎች ተገኝተዋል።

መድረኩ የህግ አውጪዎች ምስረታ እና አሰራር ዙሪያ ምክክር የሚደረግ ሲሆን ፥ የህግ አወጣጥ ሂደት እና የህግ ረቂቅ ዝግጅት ማኑዋል ቀርቦ ውይይት ይካሄድበታል ተብሏል።

በቢሾፍቱ ከተማ ዛሬ እና ነገ በሚካሄደው በዚህ መድረክ ላይ ምክር ቤታዊ ጉዳዮች ላይም ሰፋ ያለ ውውይት ይካሄዳል ተብሏል።

በምንይችል አዘዘው

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!