የሀገር ውስጥ ዜና

የአምባሳደሮች ሹመት ሙያዊ ብቃት እና ሀገራዊ ለውጥን መሰረት ያደረገ ነው – አምባሳደር ዲና

By Alemayehu Geremew

January 27, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥር 19፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ)ትናንት ለአምባሳደሮች የተሰጠው ሹመት የግለሰሰቦቹ ሙያዊ ብቃትና ክህሎት እንዲሁም ሀገራዊ ለውጥን መሰረት ያደረገ ነው ሲሉ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ገለጹ።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዛሬ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል።

አምባሳደር ዲና በመግለጫቸው ካነሷቸው ጉዳዩች መካከል፥ ትናንት በሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ለ27 አምባሳደርሮች የተሰጠውን ሹመት አንስተው ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ሹመቱ ካለፉት ጊዚያት የተለየ እና ጥናትን መሰረት ያደረገ ነው ብለዋል።

በዋናነት የግለሰሰቦችን ሙያዊ ብቃትና ክህሎት መሰረት ያደረገ እና ሀገራዊ ለውጥን መሰረት ያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል።

በተጨማሪም ሥራ እና ሰራተኛን በማመጣጠን የተሰራ መሆኑን ጠቁመው፥ በውጭ ጉዳይ ሥራ ለበርካታ ዓመታት ያገለገሉ እንደሚገኙበትም ገልጸዋል።

ከሌሎች ሀገራት ተሞክሮ በመውሰድም ከሌሎች የሙያ መስኮች ልምድ ያላቸው ግለሰቦችም ተካተዋል ነው ያሉት።

በሌላ በኩል ከተለያዩ ሀገራት እና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር በማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያ የተለያዩ የዲፕሎማሲ ስራዎች መሰራታቸውን አምባሳደር ዲና በመግለጫው አንስተዋል።

በምንይችል አዘዘው