አዲስ አበባ፣ ጥር 16፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ወይዘሮ ዳግማዊት ሞገስ፥ ከ “ዲፒ ወርልድ” ሊቀ-መንበርና ሥራ አስፈጻሚ ሱልጣን አህመድ ቢን ሱላዬም ጋር በዱባይ ፍሬያማ ውይይት ማካሄዳቸውን ገለጹ፡፡
ወይዘሮ ዳግማዊት በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፥ በቀጣይ ከአገልግሎት ሠጪ ድርጅቱ ጋር በሎጅስቲክስ ዘርፍ በትብብር መሥራት በሚቻልባቸው ሂደቶች ላይ ተወያይተው አጋርነታቸውን ለማሳደግ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ጠቁመዋል፡፡
“ዲፒ ወርልድ” መቀመጫውን በዱባይ እና በተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ያደረገ ሲሆን፥ በዓለም አቀፍ ደረጃ የጭነት፣ የወደብ እና በቴክኖሎጂ የታገዘ የንግድ ሎጀስቲክስ አገልግሎት በማቅረብ እና ንግዱን በማሳለጥ ይታወቃል፡፡