Fana: At a Speed of Life!

22 ሺህ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ተመረቀ

አዲስ አበባ መስከረም 9፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፋ ሙሁመድ በ80 ነጥብ 8 ሚሊየን ብር ወጪ የተገነባው የሺላቦ ወረዳ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ዛሬ መርቀው ከፈቱ።

የሽላቦ ወረዳ ነዋሪ ለበርካታ ዘመናት የንፁህ ውሃ እጦት የነበረበት ሲሆን፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት በክልሉ ከተያዙ የውሃ ፕሮጀክቶች ውስጥ ሽላቦ እድሉን አግኝቶ ዛሬ ለምርቃት በቅቷል ነው የተባለው።

ፕሮጀክቱ የፌዴራልና የክልሉ መንግስት በመደቡት 80 ነጥብ 8 ሚሊየን ብር ወጪ የተገነባ ሲሆን ከፕሮጀክቱ 22 ሺህ የሺላቦ ነዋሪ ተጠቃሚ ይሆናል።

ፕሮጀክቱ ከሽላቦ ወረዳ በ27 ነጥብ 5 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን መስከረም 23 ቀን 2013 ዓ.ም ተጀምሮ በአንድ ዓመት ውስጥ መጠናቀቁን የፕሮጀክቱ ተቆጣጣሪ ኢ/ር ታሪኩ ተፈራ የተናገሩት።

በፕሮጀክቱ መክፈቻ ሥነ-ስርዓት ላይ የሶማሌ ክልል የውሃ ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱረህማን አህመድ ÷ የሽላቦ ወረዳ ውሃ ፕሮጀክት ከለውጡ በፊት ሳይሰራ እንደቆየ እና አሁን ላይ የክልሉ ውሃ ልማት ቢሮ ፕሮጀክቱን ከግብ ማድረስ እንደቻለ ገልጸዋል፡፡

የኢፌዴሪ የውሃ ልማት ኮሚሽን ም/ ኮምሽነር ወ/ሮ ሸዋነሽ ደመቀ በበኩላቸው ይህ ፕሮጀክት ከተጀመሩ የውሃ ፕሮጀክቶች ውስጥ በተያዘለት ጊዜ የተጠናቀቀ ሲሆን ለሌሎችም ተምሳሌት መሆን ችሏልም ብለዋል።

ርዕሰ መስተዳድሩ በበኩላቸው÷ በአሁኑ ወቅት ሌሎች 16 ትላልቅ የውሃ ፕሮጀክቶች በግንባታ ላይ እንደሆኑ ገልፀው፣ የክልሉን ህዝብ የውሃ አቅርቦት ለማዳረስ ከፌዴራል መንግሥት ጋር እየተሰራ መሆኑን ከሶማሌ ክልል መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.