ኢጋድ በደቡብ ሱዳን ጉዳይ አስቸኳይ የመሪዎች ጉባዔ አካሄደ
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 3፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) 43ኛው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት (ኢጋድ) የመሪዎች ጉባዔ ተካሂዷል፡፡
በበይነ መረብ የተካሄደው የመሪዎች ጉባዔ በደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ያተኮረ እንደነበር ተገልጿል፡፡
በጉባዔው የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፣ የኢጋድ አባል ሀገራት መሪዎች፣ የአህጉራዊ እና ቀጣናዊ ተቋማት ሃላፊዎች ተሳትፈዋል።
ቀጣናዊ ተቋሙ ከጉባዔው በኋላ የጋራ አቋም መግለጫ ያወጣል ተብሎ እንደሚጠበቅም የኢጋድ መረጃ ያመላክታል፡፡
ኢጋድ በደቡብ ሱዳን አለመግባባቶች በውይይት እንዲፈቱ፣ ውጥረቶች እንዲረግቡ እና የደቡብ ሱዳን ሕዝብ መጻኢ ጊዜው ሰላም እንዲሆን የጀመረውን ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስገንዝቧል፡፡