Fana: At a Speed of Life!

የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት ቅርስ ጥገና ጥንታዊነቱን በጠበቀ አግባብ እየተከናወነ ነው

አዲስ አበባ፣ መስከረም 10፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት ቅርስ የጥገና ስራ ታሪካዊነቱንና ጥንታዊነቱን በጠበቀ አግባብ እየተከናወነ መሆኑን የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ።

የቢሮው የማኔጅመንት አባላት የቅርሱ የጥገና ስራ ያለበትን ሁኔታ ዛሬ ተዘዋውረው በጎበኙበት ወቅት የቢሮው ሃላፊ መልካሙ ጸጋዬ፤ የቅርስ ጥገና ስራው የጎንደር ከተማን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ተናግረዋል።

መንግስት ለቅርሱ ጥገናና ልማት ስራ የሰጠው ልዩ ትኩረት የህዝቡን ታሪክና ባህል ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ ባለው ቁርጠኝነት እንደሆኑ ገልጸዋል።

የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት ቅርስ የጥገና ስራ ታሪካዊነቱንና ጥንታዊነቱን በጠበቀ አግባብ እየተከናወነ መሆኑን ማረጋገጣቸውን ጠቁመው፤ ጥገናው ሲጠናቀቅ ከተማዋን ተመራጭ የቱሪስት መናኸሪያ ለማድረግ እንደሚያስችል ተናግረዋል።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አመራር ሰጪነት እየተካሄደ ያለው የቅርሱ ጥገና በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ የጎንደር ከተማ ህዝብ እያደረገ ያለው ትብብር ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አመልክተዋል።

የጥገና ስራው በተያዘለት ጊዜ ተጠናቆ ለጎብኚዎች ክፍት እንዲሆንም የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን የቅርብ ድጋፍና ክትትል እያደረገ እንደሚገኝ መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

የጎንደር ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ አቶ ዮናስ ይትባረክ በበኩላቸው፤ የፌደራልና የክልሉ መንግስት የቅርስ ጥገና ስራው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ በልዩ ትኩረት እየደገፉ ናቸው ብለዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.