Fana: At a Speed of Life!

በትግራይ ክልል የተከሰተውን የአምበጣ መንጋ ለመከላከል የተቋቋመው ግብረ-ሃይል ስራ ጀምሯል

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 7፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በትግራይ ክልል የተከሰተውን የአምበጣ መንጋ ለመከላከል በክልል ደረጃ ግብረ-ሃይል ተቋቁሞ ስራ መጀመሩን የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ-መስተዳድር ጌታቸው ረዳ አስታወቁ።

ህብረተሰቡ በሰብልና ደን ላይ የተከሰተውን የአምበጣ መንጋ በመከላከል ሂደት ተሷትፎውን አጠናክሮ እንዲቀጥልም አሳስበዋል።

አቶ ጌታቸው ረዳ ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት÷ በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች በሚባል ደረጃ የአምበጣ መንጋ ተከስቷል።

መንጋው አሁን ላይ በመኸር ሰብልና በደኖች ላይ በመስፈር ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ጠቁመው÷ ህብረተሰቡ በየአካባቢው በባህላዊ ዘዴ መንጋውን እየተከላከለ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

የአምበጣ መንጋው ከአቅም በላይ እየሆነ በመምጣቱ በክልል ደረጃ ግብረ-ሃይል ተቋቁሞ የመከላከል ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል።

የአምበጣ መንጋውን ከምንጩ መከላከል የሚያስችል የኬሚካልና የአውሮፕላን ድጋፍ ከፌዴራል መንግስት እንዲደረግ ስራዎች መጀመራቸውን አቶ ጌታቸው መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.