Fana: At a Speed of Life!

ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት ሀገራዊ የደኅንነት ሁኔታን በመገምገም አቅጣጫዎችን አስቀመጠ

 

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 2፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው ስብሰባ ሀገራዊ የደኅንነት ሁኔታን በመገምገም የተለያዩ አቅጣጫዎችን አስቀመጠ።

ምክር ቤቱ በስብሰባው በቀደሙት ወራት ተለይተው የነበሩ ሀገራዊ ሥጋቶችን መሠረት በማድረግ የተከናወኑ ተግባራትንና ያጋጠሙ ውስንነቶችን ለግምገማው መነሻ ማድረጉን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

የምክር ቤቱ መግለጫ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፡-

የተከበራችሁ የሀገራችን ሕዝቦች፣
ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው ስብሰባ ሀገራዊ የደኅንነት ሁኔታ የገመገመ ሲሆን፣ በቀደሙት ወራት ተለይተው የነበሩ ሀገራዊ ሥጋቶችን መሠረት በማድረግ የተከናወኑ ተግባራትንና ያጋጠሙ ውስንነቶችን ለግምገማው መነሻ አድርጓል። የደኅንነት ምክር ቤቱ ሰኔ 1 ባካሄደው ስብሰባው ወቅት በአስቸኳይ ለማከናወን ተወስነው ከነበሩ ተግባራት መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡-
1. አሸባሪና የታጠቁ ቡድኖችን በአመራራቸው ላይ ትኩረት በማድረግ ለመደምሰስ፣
2. ለጠላት ዐቅም የሚሆነው ከዳተኛ የጸጥታ ኃይል ስለሆነ፣ የዚህን ምክንያት፣ መነሻና ዋና ዋና ተዋንያን ለመለየት፣
3. ልዩ ልዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን እያወያዩ፣ በዓላማና በተግባር ላይ እየተግባቡ፣ የጋራ ተግባርን ለማቀናጀትና ግጭቶችን ትርምስ
አልባ ወደሚሆኑበት መጠን ለመቀነስ፣
4. የሥጋት መነሻና የሥጋት ተዋንያን የሆኑ አካላትን ለማወያየትና ራሳቸውን ከሥጋት መነሻነትና ከሥጋት ተዋናይነት እንዲነጥሉ ለማድረግ፣
5. የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደቀድሞ አካባቢያቸው በመመለስ ለማቋቋም፤ የፈረሱ የመንግሥት መዋቅሮችን መልሶ ለማደራጀትና ሥራ
እንዲጀምሩ ለማድረግ፣
6. ኮንትሮባንድ፣ የኢኮኖሚ አሻጥር፣ ግድያ፣ ዝርፊያ፣ ኢመደበኛ አደረጃጀት፣ ወዘተ. ዓይነት ሕገ ወጥ እንቅስቃሴዎችን ከሥራቸው ነቅሎ ለማስቆም፣
7. የፍትሕና የጸጥታ ተቋማትን ለማስተካከል አቅጣጫዎች ተቀምጠው ነበር።
እነዚህን አቅጣጫዎች መሠረት በማድረግ የተከናወኑ ተግባራትን የተመለከተው የደኅንነት ምክር ቤቱ እጅግ ወሳኝ፣ ችግር ፈቺ፣ ተግዳሮቶችን የሚቀንሱ፣ ሰላምና ጸጥታን ለማስፈንና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎቻችንን ለማሳለጥ የሚጠቅሙ ተግባራት በክልሎችና በፌዴራል ደረጃ እየተከናወኑ መሆኑን አድንቋል።
በኦሮሚያ ክልል ሸኔን ለመደምሰስ የሚያስችሉ የሸዋ፣ የወለጋ፣ የጉጂ ኮማንድ ፖስቶች የተደራጁ ሲሆን፤ መከላከያ፣ የክልሉ አመራርና የክልሉ የጸጥታ ኃይሎች በጋራ የተቀናጀ ሥምሪት እያካሄዱ ይገኛሉ። በዚህም 3180 የሸኔ ታጣቂዎች በቁጥጥር ሥር የዋሉ ሲሆን እጃቸውን ላለመስጠት አሻፈረኝ ያሉት ተደምስሰዋል። በተጨማሪም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የአባ ቶርቤ፣ የአልሸባብና የጁንታው ሴሎችና ተባባሪዎች ተይዘዋል።
በኦፕሬሽኑ በርካታ የነፍስ ወከፍና የቡድን መሣሪያዎች፣ ተተኳሾች፣ ተሽከርካሪዎች፣ ገንዘብና ልዩ ልዩ ንብረቶች ከጠላት ተማርከዋል።
በጠላት ተይዘውና ፈርሰው ከነበሩ 1,739 ቀበሌዎች መካከል 1,255 ያህሉ እንደገና ተደራጅተዋል። 252,129 የቤተሰብ አባላትን የያዙ 47,558 አባዎራዎች ወደ ቀድሞ ቀያቸው ተመልሰዋል።
በተመሳሳይ በአማራ ክልል ሕግን ለማስከበር በተወሰደው የተቀናጀ የጸጥታ ኃይሎች፣ የአመራሩና የሕዝቡ ሥምሪት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተጠርጣሪዎች በሕግ ጥላ ሥር ውለዋል። ከእነዚህ መካከል ገሚሱ የጸጥታ ኃይሎችን በመክዳት ለሕገ ወጥ ታጣቂዎች ዐቅም ሲፈጥሩ የቆዩ ሲሆኑ፣ የተቀሩት በልዩ ልዩ ወንጀሎች ሲፈለጉ የከረሙ ናቸው።
ከወያኔ ጋር ወግነው በክልሉ የሚኖሩ ሕዝቦችን እርስ በእርስ ለማጋጨት የሚሰሩ ታጣቂዎች ላይ ርምጃ የተወሰደ ሲሆን፣ ጠላት ተጨማሪ ሰው የማያገኙበት ደረጃ ላይ ለማድረስ እየተሠራ ነው። ከቅማንት ሕዝብ ጋር በተገናኘ የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት እንዲሁም በኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን ተከስቶ የነበረውን ጸጥታ ችግር እንዳይባባስ ለማድረግ የውይይት መድረኮች ተዘጋጅተው የተሻለ መግባባት ተፈጥሯል፡፡
በአጠቃላይ በክልሉ እስካሁን ድረስ ከ6.6 ሚልዮን በላይ ሕዝብ የተሳተፈባቸው የውይይት መድረኮች የተካሄዱ ሲሆን፣ በ633 አመራሮችና ባለሞያዎች ላይም ከመጀመሪያ ማስጠንቀቂያ ጀምሮ በሕግ ቁጥጥር ሥር እስከማዋል የደረሰ ርምጃ ተወስዷል።
በአዲስ አበባ ከተማ የሕዝብን ጸጥታና ደኅንነት ከማረጋገጥ አንጻር መልካም ተግባራት መከናወናቸውን የደኅንነት ምክር ቤቱ በግምገማው ተረድቷል።
ከ497 በላይ የጁንታው፣ የሸኔ፣ የአልሸባብና ሌሎች አክራሪ ቡድኖች በቁጥጥር ሥር ውለዋል። ከእነርሱም ጋር የጸጥታ ኃይሎች አልባሳት፣ ሐሰተኛ መታወቂያዎች፣ ማኅተሞች፣ ለሽብር ተግባር የተዘጋጁ ሰነዶች፣ የኤሌክትሮኒክስ መሣሪያዎች፣ የጦር መሣሪያዎች፣ ተሸከርካሪዎች፣ ለአሸባሪዎች ሊላኩ የነበሩ ተንቀሳቃሽ ስልኮች እና የባንክ ደብተሮች አብረው በቁጥጥር ሥር ውለዋል።
የተደራጁ ወንጀሎችን ሲመሩ የነበሩ 314 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር የዋሉ ሲሆን፣ 75 ከተማና የፌዴራል መንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በሙስና ተጠርጥረው ተይዘዋል።
በመሬት ወረራ የተወሰዱ መሬቶችን ማስመለስ እና ሕገወጥ ግንባታ የተፈጸመባቸው በጥቅሉ በ1596 ቦታዎች ላይ እርምጃ መውሰድ ተችሏል።
በአዲስ አበባ የተሠራው ሥራ ውጤት ማምጣቱን የደኅንነት ምክር ቤቱ ያረጋገጠ ሲሆን÷ የፍትሕ አካላትን ከማጥራት አንጻር በበቂ ሁኔታ እንዳልተሠራ ገምግሟል፡፡
በተጨማሪም በከተማዋ የሚደረጉ የሕዝብ ውይይቶች በበቂ መተማመን የፈጠሩ አለመሆናቸውን፤ በሽብር እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳታፊ የሆኑ አካላትን ከዚህ በላይ ማጋለጥና መቆጣጠር እንደሚገባ፤ ሙስናና የኢኮኖሚ አሻጥርን መልክ ለማስያዝ በሙሉ ኃይልና በቁርጠኝነት መሥራት እንደሚያስፈልግ ምክር ቤቱ አሥምሮባቸዋል።
በቤኒሻንጉል ጉምዝ ያለው የሥጋት ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ፣ ሰላምና ደኅንነት ይበልጥ እየተረጋገጠ መምጣቱን ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤቱ ተመልክቷል። በክልሉ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሕገ ወጥ ታጣቂዎች የተደመሰሱ ሲሆን፣ 1,826 የሚደርሱ ታጣቂዎች በቁጥጥር ሥር ውለዋል።
749 ልዩ ልዩ የጦር መሣሪያዎች እና 5,639 ተተኳሾች ከጠላት የተማረኩ ሲሆን፣ 9 ጀልባዎችና 65 የጠላት ካምፖችም ወድመዋል። እጃቸውን በሰላም የሰጡ ሕገወጥ ታጣቂዎችን ወደ መደበኛ ሕይወት የማስገባት እንዲሁም፤ በከማሺና በመተከል ዞኖች 171,485 ተፈናቃዮችን የማቋቋም ሥራ ተሠርቷል።
ከጠላት ነጻ ከወጡ 180 ቀበሌዎች መካከል በ169ኙ የመንግሥት መዋቅር መልሶ ተደራጅቷል።
በክልሉ አንጻራዊ ሰላም መስፈኑን፣ የሽፍታ ቡድኖች ዐቅም መዳከሙን፣ ተፈናቃዮችን መልሶ የማቋቋም ተግባር እየተሻሻለ መሄዱን፣ የደኅንነት ምክር ቤቱ በአዎንታዊነት የገመገመ ሲሆን፣ በቀጣይ ሊከናወኑ የሚገቡ ያልተጠናቀቁ ተግባራት መኖራቸውንም አይቷል።
ከእነዚህም መካከል ከሸኔና ከጁንታው ጋር እየተቀናጀ በድንበር አካባቢ የሚንቀሳቀሰውን የሽፍታ ቡድን ሙሉ በሙሉ የመደምሰስ፤ የመንግሥትን መዋቅር መልሶ ወደ ሥራ የማስገባት፤ በሰላም የገቡትን ታጣቂዎች ወደ ሰላማዊ ሕይወት እንዲመለሱ የማቋቋም ተግባራት ይገኙበታል። የክልሉ አመራሮች፣ የጸጥታ ኃይሎችና ሕዝቡ እነዚህን ተግባራት በቀሪ ጊዜያት እንደሚያከናውኗቸው ምክር ቤቱ የጸና እምነቱ መሆኑን አመልክቷል።
በደቡብ ክልል እየተከናወነ የሚገኘው ሰላምንና ደኅንነትን የማረጋገጥ ሥራ ካለፉት የተሻለ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን የደኅንነት ምክር ቤቱ ገምግሟል። ከብሔረሰቦች የሚነሡ የአደረጃጀት ጥያቄዎችን የመለየትና ለሀገርና ለሕዝብ ዘላቂ ጥቅም በሚያስገኝ መንገድ ለመፍታት እየተሠራ ነው።
ጥያቄዎችን ለመፍታት የሚያስችል ሁኔታ በመፈጠሩ በኢመደበኛነት ተደራጅቶ ጫና የሚፈጥር ኃይል ወደ ሰላማዊ ሁኔታ እየተመሰለ ነው።
በአዋሳኝ አካባቢዎች የሚታየውን የሸኔ እንቅስቃሴ ከአጎራባች ክልሎች ጋር ተቀናጅቶ የማስወገድ፤ ከክልል መደራጀት ጋር የሚነሡ ጥያቄዎችንና ቅሬታዎችን አስቀድሞ በመለየት በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ማገዝ፤ የአከላለል ጥያቄዎችን ለሕገ ወጥ ተግባራት መጠቀሚያነት እንዳይውሉ ፍላጎት ያላቸው ተዋንያንን አስቀድሞ በመለየት ተገቢውን ርምጃ መውሰድ እንደሚገባ የደኅንነት ምክር ቤቱ አቅጣጫ ሰጥቷል።
በሶማሌ ክልል ከውጭና ከውስጥ የሚመነጩ የደኅንነት ሥጋቶችን ለመከላከል፣ ለመቋቋምና ለማስወገድ ወሳኝ ተግባራት መከናወናቸውን የደኅንነት ምክር ቤቱ በግምገማው አረጋግጧል።
ሐምሌ 14 ቀን በአፍዴር ዞን በባሬና ጎት ጎት ወረዳዎች ሠርጎ ለመግባት የሞከረውን የአልሸባብ ኃይል ተከታትሎ ለመደምሰስ የክልሉ ልዩ ኃይል ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል።
የክልሉ አመራር ሕዝቡን በማንቃት፣ በማሳተፍና በማደራጀት ጠላትን ለመደምሰስ ትምህርት ሰጪ እንቅስቃሴ አድርጓል። በሂደት የሀገር መከላከያ ሠራዊት የተሳተፈበት ኮማንድ ፖስት የተቋቋመ ሲሆን፣ በተካሄደ ኦፕሬሽን 813 አሸባሪዎች ተገድለው 79 ተማርከዋል። ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የጦር መሣሪያዎች፣ ተተኳሽ ጥይቶች፣ ፈንጂዎችና መገናኛ ሬዲዮኖች ተማርከዋል።
ኮንትሮባንድን ለመቆጣጠር የሥጋት መሥመሮችን በመለየት ኬላዎች እየተጠናከሩ ቢሆንም አሁንም ሕገ ወጥ ተግባሩን በሚገባ ለመቆጣጠር አለመቻሉን፤ በጎሳዎች መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶችን ለመፍታት የጎሳ መሪዎችና አመራሩ በሚገባቸው ልክ አለመንቀሳቀሳቸውን፤ በጸጥታ ሥምሪት አፈጻጸም ላይ የሚታዩት የዲሲፕሊን ግድፈቶች መኖራቸውን፤ የአልሸባብን ሥጋትን በማስወገድ የውስጥ ደኅንነትን ለማረጋገጥ አሁንም የሚቀሩ ሥራዎች መኖራቸውን የደኅንነት ምክር ቤቱ በግምገማው አመላክቷል።
በአፋር ክልል የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴን ለመቆጣጠር እየተሠራ መሆኑን የደኅንነት ምክር ቤቱ የገመገመ ሲሆን፣ በተለይም ዋናውን የኢትዮ-ጂቡቲ መሥመር ደኅንነት በማረጋገጥ በኩል ወሳኝ ሥራ መሠራቱን፤ ከአጎራባች ክልሎች ጋር በመነጋገር የጸጥታ ችግሮችን ለመፍታት እየተሞከረ መሆኑን ምክር ቤቱ በአዎንታ ተቀብሎታል። በአንጻሩ የጠላት እጅ የተጨመረበት የኮንትሮባንድ ንግድ አሠራሩን እየቀያየረ፣ አድማሱን እያሰፋ መምጣቱን፤ በጸጥታ ኃይሎች መካከል የቅንጅት ክፍተት መኖሩን፤ የጎሳ ግጭቶችን በኃላፊነት መንፈስ ለመፍታት የሚያስችል ሥራ በበቂ ሁኔታ አለመከናወኑን ምክር ቤቱ ገምግሟል። በመሆኑም በቀጣይ እነዚህ ወሳኝ ጉዳዮች ትኩረት አግኝተው፣ ተገቢ ውጤት ለማምጣት በሚያስችል ሁኔታ እንዲፈጸሙ አቅጣጫ አስቀምጧል።
ውድ ኢትዮጵያውያን፣
በትግራይ ክልል ያለው ሁኔታ በሰላማዊ መንገድ በድርድር እንዲፈታ መንግሥት አቅጣጫ መያዙና የተግባር እንቅስቃሴ ማድረጉ የአደባባይ እውነታ ነው። ድርድሩ ውጤት እስኪያመጣ ድረስ ለመቀጠል መንግሥት ቁርጠኛ መሆኑን ወዳጅም ጠላትም ተረድቶታል።
በዚያ አካባቢ ያለውን የሥጋት ሁኔታም ከቀረበለት ሪፖርት በመነሣት የደኅንነት ምክር ቤቱ የገመገመ ሲሆን፤ ሁኔታዎች ከጸጥታ አካላት ዐቅም በታች መሆናቸውንና በተገቢው መንገድ ክትትል እየተደረገባቸው መሆኑን አረጋግጧል። ከግምገማው በመነሣት በአመራሩና በጸጥታ አካላት ሊከናወኑ የሚገባቸውን ተግባራት በመለየት አቅጣጫዎችን አስቀምጧል።
በአጠቃላይ የውስጥ ተጋላጭነትን በመቀነስ፣ ሀገራዊ ደኅንነትን ከማረጋገጥ አንጻር ከፍተኛ አዎንታዊ ለውጥ መምጣቱን፣ የፀጥታና ደኅንነት ጉዳይ ለመንግስት ብቻ የሚሰጥ አለመሆኑን በመገንዘብ ሕዝቡም የሥራው ባለቤት እየሆነ መምጣቱን ከግምገማው ለመገንዘብ ተችሏል።
በሌላ በኩል ሥራዎች ገና አለመጠናቀቃቸውን፤ የጸጥታና ደኅንነት መዋቅሩ በሚጠበቀው መጠን አለመጥራቱን፤ የአመራሩንና የሕዝቡን የጸና ሥነ ልቡና የመገንባት ሥራ በተገቢው ልክ አለመሠራቱን፤ ጁንታው ከውስጥና ከውጭ ኃይሎች ጋር ሊያደርገው የሚፈልገውን ቅንጅት ለማምከን በልኩ አለመሠራቱን የደኅንነት ምክር ቤቱ ተመልክቷል።
እነዚህ ጉዳዮች በተገቢው ትኩረትና ቁርጠኝነት ካልተሠሩ የተገኘው አንጻራዊ ሰላም ዘላቂ እንደማይሆን ገምግሟል።
በመሆኑም የሚከተሉት ተግባራት በአመራር፣ በጸጥታ አካላትና በሕዝቡ ቁርጠኝነትና መሥዋዕትነት ሊተገበሩ እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጧል።
1. አሸባሪና ሕገ ወጥ ታጣቂዎችን ሥጋት ከማይሆኑበት ደረጃ ማድረስ፣
2. ሕዝብን በማወያየት፣ የታጠቁ አካላትን በማግባባት፣ ወጣቶችን በሰላም ተግባራት ላይ በማሳተፍ፣ ዘላቂ ሰላም የሚያረጋግጡ ሥራዎችን መሥራት፣
3. የፍትሕ አካላትን በማጥራትና በማጠናከር ለሀገራዊ ሰላምና ደኅንነት የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ማድረግ፣
4. ሕዝቡን በሚያማርሩ የኢኮኖሚ አሻጥር፣ የሙስና፣ የኮንትሮባንድ፣ ሕገወጥ የገንዘብ ዝውውር ወዘተ ላይ የማያዳግም ርምጃ በመውሰድ ሕዝቡ እፎይ እንዲል ማድረግ፣
5. በየደረጃው ያለውን አመራር በማጥራትና ተጠያቂነትን በማስፈን፤ በየደረጃው ብቁ፣ ንቁና ወትሮ ዝግጁ የሆነ አመራር መፍጠር፣
6. ሕዝባዊና የሃይማኖት በዓላትን፣ የብሔርና የአስተዳደር እርከን ጥያቄዎችን፣ ጠላት የዓላማው ማስፈጸሚያና የሕዝቡን ሰላም ማወኪያ እንዳያደርጋቸው፣ ከሚመለከታቸው ጋር በመቀናጀት መሥራት፣
7. በአፋርና በዒሳ መካከል፣ በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን የሚታዩ የጸጥታ ሥጋቶችን በዘላቂነት ለመፍታት ተገቢውን የፖለቲካና የጸጥታ ሥራ መሥራት፣
8. አልሸባብ ከውጭና ከውስጥ ኃይሎች ጋር ተቀናጅቶ የሥጋት መጠኑን ለመጨመር እንዳይችል፣ የተቀናጀ የጸጥታ ኃይሎችና የሕዝብ ሥምሪት ማካሄድና በቀጣናው ትርጉም ያለው ኃይል እንዳይሆን ማድረግ ቀጣይ ተግባሮቻችን ናቸው።
አመራሩ፣ የጸጥታ መዋቅሩና ሕዝቡ ተግባብቶና ተቀናጅቶ ሲሠራ ምን ዓይነት አመርቂ ውጤት እንደሚመዘገብ ካለፉት ሥራዎቻችን በሚገባ ተምረናል። በቀጣይም ይሄንኑ አጠናክሮ መቀጠል ያስፈልጋል።
እያንዳንዱን ተግባር ቆጥሮና ኃላፊነት ወስዶ ማከናወን፣ በየጊዜው መገምገም፣ የሠሩትን ማበረታታትና ኃላፊነታቸውን የማይወጡትንም መቅጣት ይገባል።
በእያንዳንዱ አካባቢ የሚከናወነው ጸጥታንና ደኅንነትን የማረጋገጥ ተግባር የመላዋ ኢትዮጵያ ሰላም የሚያጸና መሆኑን ማመን ያስፈልጋል። አጠቃላዩ ነገር የቅንጣቶቹ ድምር ውጤት፣ አንዳንዴም ከቅንጣቶቹ ድምር በላይ ነው።
አጠቃላዩን የጸጥታና የደኅንነት ሁኔታ የተሻለ ለማድረግ እያንዳንዳችን በተሠማራንበት መስክ የምናከናውን ቅንጣት ተግባር በጥራትና በብቃት መወጣት ይገባናል።
ሕዝባችን ሰላሙና ደኅንነቱ ተረጋግጦለት ኢትዮጵያን ለማበልጸግ በሚደረገው ርብርብ ንቁ ተሳታፊ እንደሚሆን በየደረጃው በተካሄዱ ውይይቶች በአንድ ቃል ተናግሯል። በየጊዜው የምናደርጋቸው የግምገማ ውይይቶች፣ አዳዲስ ምክንያቶችን የምንሰማባቸው ሳይሆኑ፣ የችግሮችን መቀነስና የሰላምና ደኅንነትን መስፈን የሚያረጋግጡ መሆን አለባቸው።
ይህ ደግሞ የሚሳካው ዕቅድን በሚገባ በመገንዘብ፣ የሚያስፈልገውን ሥምሪት በማካሄድና እስከ መጨረሻው ድረስ ለውጤቱ ብቻ በመድከም ነው። ስለሆነም በየደረጃው ያሉ አመራሮች፣ የጸጥታ ኃይሉና ሕዝቡ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ፣ እንደ አንድ ልብ መካሪ ሆኖ የኢትዮጵያን ጸጥታና ደኅንነት ለማረጋገጥ እና ብልጽግናዋን እውን ለማድረግ ቁርጠኞች እንድንሆን ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤቱ ጥሪ ያቀርባል።
የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት
ነሐሴ 2፣ 2014 ዓ.ም
አዲስ አበባ
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.